ለበቀል የተነሳች ሴት በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የመንገድ ትራንስፖርት ቢሮ የስምሪት ዳይሬክቶሬት ዳይሬከተር ላይ የአሲድ ጥቃት ፈጽማለች፡፡
ግለሰቧ የስራ ሀላፊው ላይ የአሲድ ጥቃት የፈጸመችው ነሐሴ 02 ቀን 2011 ዓ.ም በባህር ዳር ከተማ ነው ተብሏል፡፡
የባሕር ዳር ከተማ 3ኛ ፖሊስ ጣቢያ የምርመራ የሥራ ሂደት አባል የሆኑት ምክትል ኢንስፔክተር ይስማው ታሪኩ ተጠርጣሪዋ ጥቃቱን ለመፈጸም አሲድ ገዝታ ነሐሴ 2 ቀን 2011 ዓ.ም ጠዋት ላይ ወደ ዳይሬክተሩ ቢሮ እንደሄደች ነገር ግን ስብስባ ላይ ናቸው ተብላ እንደተመለሰች ፤
ከሰዓት በኋላ ስትመለስ ግን የስራ ሀላፊው ቢሯቸው ውስጥ በሥራ ላይ እንዳሉ እንዳገኝቻቸውና በጆግ ይዛው የመጣችውን አሲድ ከቅርብ እርቀት ላይ ሆና እንደደፋችባቸው ከዚያም ምን እንደተከሰተ መለስ ብላ ሳታይ እሩጣ እንደወጣች ቃሏን ለፖሊስ ሰጥታለች ብለዋል፡፡
ተጠርጣሪዋ ድርጊቱን ፈጽማ ለማምለጥ ብትሞክርም በአካባቢው በነበሩ ሰዎች ትብብር በቁጥጥር ሥር የዋለች ሲሆን ጥቃቱ የተፈጸመባቸው የስራ ሀላፊም ወዲያውኑ ወደ ሐኪም ቤት ተወስደው ህክምና እንዲያገኙ ተደርጓል ተብሏል።
የክልሉ የመንገድ ትራንስፖርት ቢሮ የስምሪት ዳይሬክቶሬት ዳይሬከተር አቶ ደመላሽ ስንሻው በተፈጸመባቸው የአሲድ ጥቃጥ በሁለት እጆቻቸው እና ሆዳቸው አካባቢ የመጥቆርና የማበጥ እንዲሁም ፊታቸው ላይ አልፎ አልፎ የመቃጠል ጉዳት ደርሶባቸዋል ተብሏል፡፡
ተጠርጣሪዋ ጥቃቱን ለመፈጸም የተጠቀመችበትን አሲድ ለመኪና ባትሪ በሚል እንደገዛችው ለፖሊስ የተናገረች ሲሆን ፖሊስም የአሲዱን ምንጭ ለማወቅ ምርመራ እያደረገ መሆኑን ተናግሯል።
ምክትል ኢንስፔክተር ይስማው ታሪኩ ግለሰቧ በ2008 ዓ.ም በህጋዊ መንገድ ‘እፎይታ’ በሚባል ማህበር የተመዘገበ ባጃጅ መግዛቷን እና በዚህም ለተወሰነ ግዜ የስምሪት መርሃ ግብር ወጥቶላት ባጃጇ በሥራ ላይ ተሰማርቶ መቆየቱን ተናግረዋል።
ኢንስፔክተር ይስማው ጨምረውም “በኋላ ላይ ተጠርጣሪዋ ‘ምክንያቱን አላውቀውም’ በምትለው ሁኔታ የማህበሩ ታፔላ እንዲነሳ ተደርገ፤ ባጃጇም እንድትያዝ ተደረገች” ይላሉ።
ግለሰቧ ይህ እንዲሆን ያደረገው ቀደም ሲል የባሕር ዳር መንገድ ትራንስፖርት ጽህፈት ቤት ኃላፊ የነበሩት እና አሁን የክልሉ መንገድና ትራንስፖርት ቢሮ የስምሪት ዳይሬክቶሬት ዳይሬከተር የሆኑት አቶ ደመላሽ ስንሻው ናቸው ብላ ማሰቧን ፖሊስ ተናግሯል።
ጥቃቱ የተፈጸመባቸው አቶ ደመላሽን በሥራቸው ግለሰቧን ኢላማ እንዳላደረጉና ሌሎችም ከስምሪት ቦታቸው ውጪ የሚሰሩ ባጃጆችን ሥርዓት ለማስከበር ሲባል ሌሎችም እንደተያዙ ለፖሊስ ተናግረዋል።
ስሞኦን ደረጀ