
በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ በላስቲክ በተሰራ ቤት ውስጥ በተደረገ ብርበራ በርካታ ሀሰተኛ ሰነዶች እና ማህተሞች ከነተጠርጣሪው በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡
በአዲስ አበባ ፖሊስ የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት፣ ከፌዴራል ፖሊስና ከህብረተሰቡ ጋር በመቀናጀት በክፍለ ከተማው ወረዳ 1 ልዩ ቦታው አሜሪካን ግቢ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ አንድ ግለሰብ ላስቲክ ወጥሮ በሚኖርበት ቤት ውስጥ በተደረገ ብርበራ ነው ሃሰተኛ ሰነዶቹ በቁጥጥር ስር ሊውሉ የቻሉት፡፡
ተጠርጣሪው ግለሰብ የሽብር ቡድኖቹን እኩይ አላማ ለማስፈጸም እና ለሰርጎ ገቦች ሽፋን ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር በማሰብ እና ህገ- ወጥ ተግባራት እንዲስፋፉ ተባባሪ በመሆን ድርጊቱን በድብቅ ሲፈፅም እንደቆየ ከክፍለ ከተማው ፖሊስ መምሪያ የወንጀልና ትራፊክ አደጋ ምርመራ ምክትል ዳይሬክቶሬት የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
የፀጥታ አካላቱ በህዝብ ጥቆማ መነሻነት ባደረጉት ክትትል እና ባከናወኑት ብርበራ ከላስቲክ ቤቱ ውስጥ በርካታ ሀሰተኛ የትምህርት ማስረጃዎች፣ ፖስፖርቶች፣ የተለያዩ ክልሎች የቀበሌ መታዎቂያዎች፣ ሌሎች ልዩ ልዩ ሰነዶችና ማህተሞች ተገኝተዋል፡፡
የከተማዋን ሠላምና ደህንነት ለማስጠበቅ ህብረተሰቡ ከፀጥታ አካላቱ ጋር ተቀናጅቶ እየሰራ ያለው ስራ ይበል የሚያሰኝ እንደሆነና በተለይም በአሁኑ ወቅት የሽብር ቡድኖቹ ለሚያሰራጩት የሀሰት መረጃ ጆሮ ባለመስጠት የተለመደ ትብብሩን አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ሲል ፖሊስ ጥሪውን አቅርቧል።
ምንጭ፦ አዲስ አበባ ፖሊስ