በተለያዩ አካባቢዎች ከሰሞኑ በአዲስ አበባ በስፋት የሚስተዋለዉ ጉንፋን መሰል የጤና እክል ኮቪድ ሊሆን እንደሚችል የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ በርካታ ሰዎች በጉንፋን መታመማቸዉን እየተናገሩ እንደሆነና ይህንንም ተመልክተናል ሲሉ በጤና ሚኒስቴር የኮቪድ-19 ምላሽ ግብረ ሃይል አስተባባሪ ዶክተር መብራቱ ማሴቦ ለብስራት የተናገሩ ሲሆን በሰሞኑ በስፋት የሚታየው ጉንፋን መሰል የጤና እክል ኮቪድ19 የመሆን እድሉ ሰፊ ነው ብለዋል፡፡
በዓለም ላይ የሚገኙ ከ89 ሀገራት በላይ ኦሚክሮን የተባለው አዲሱን ልውጥ የኮሮና ቫይረስ መከሰቱን እና በኢትዮጲያም ይህ ቫይረስ ስለመከሰቱ የሚያጠራጥሩ ምልክቶች እየታዩ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ከሰሞኑ በአዲስ አበባ እየታየ የሚገኘው ጉንፋን መሰል ነገር ደጋግሞ ማስነጠስ፣ ትኩሳት፣ብርድ ብርድ ማለት እና የራስ ምታት ከኦሚክሮን ምልክቶች ጋር እንደሚያመሳስለው ዶክተር መብረሀቱ አስረድተዋል፡፡በኢትዮጲያ በኮሮና ቫይረስ በቀን የሚያዘው የሰው ቁጥር እየጨመረ መሆኑን የተነገረ ሲሆን ያልተከተቡ ሰዎች የመያዝ እድላቸው አሁንም ሰፊ መሆኑን እና የተከተቡ ሰዎች በቫይረሱ ቢያዙ እንኳን ህመሙ እንደማይበረታባቸው እና ለሞት የመዳረግ እድሉ ጠባብ እንደሆነ መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡
በትግስት ላቀው