በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 ልዩ ስሙ ቱሪስት ኮንዶሚኒየም አካባቢ በግለሰብ ቤት ውስጥ በሁለት መጋዘን በሕገ-ወጥ መንገድ የተደበቀ ብዛት ያለው የሲጋራ ምርትና የመገናኛ ሬድዮ በፀጥታ ኃይሎች ተይዟል፡፡
በህብረተሰቡ ጥቆማ ብዛቱ 465 ካርቶን “ሻምላን” እና “ጎልደን” ሲጋራ፣ 5 ኩንታል ስኳር ፣ ኦባማ የጭነት መኪና እንዲሁም 1 የመገናኛ ሬድዮ በፀጥታ ኃይሎች መያዙ ተገልጿል፡፡
እንደዚህ አይነት ሲጋራዎችን ማዘዋወርም ሆነ ወደ ሐገር ውስጥ ማስገባት እንደማይቻል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምግብ መድሀኒት ቁጥጥር ባለስልጣን የጤና ጉዳዮች ተቆጣጣሪ አቶ አሸናፊ ደመቀ ተናግረዋል።
የየካ ክፍለ ከተማ ምግብና መድሀኒት ቁጥጥር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ብርሀን መንገሻ በበኩላቸው፥ ሲጋራ ዘርፈ ብዙ ጉዳት ያለው መሆኑን ገልፀው ለህብረተሰቡ ጥቆማ ምስጋና ማቅረባቸውን ብስራት ሬድዮ ከክፍለ ከተማው ኮሙኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡