በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ፊቼ ከተማ መስተዳድር የኢትዮ ቴሌኮም የመስመር ሽቦ የሰረቁ 13 ግለሰቦች በቁጥጥር ስር መዋላቸው ተገልጿል።በፊቼ ከተማ አራት ቀበሌዎች የኢትዮ ቴሌኮም የመስመር ሽቦ የሰረቁ እና በቤታቸው ያካማቹ 13 ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው የክስ መዝገባቸው በመጠራት ላይ መሆኑ የፊቼ ከተማ መስተዳድር ፖሊስ ፅ/ቤት የአካባቢ ሰላም ማስከበር የስራ ሂደት ባለቤት ሳጅን ኩማ ሀይሉ በተለይ ለብስራት ሬዲዮ ተናረዋል፡፡
የመሰረተ ልማት ላይ የሚካሄደው ስርቆት እና ዘረፋ በዋናነት ለግል ጥቅም የሚከናወን ቢሆኑም ጉዳቱ በሀገር እና በማህበረሰብ ላይ ያነጣጠረ መሆኑን ፖሊስ በትኩረት እየሰራበት እንዳለ ተናግረዋል፡፡ተጠርጣሪዎቹን ለፍትህ አካል ለማቅረብ ያለውን ውስን ክፍተቶችን ለመቅረፍ እየተሰራ አጥፊዎችን ደግሞ ለፍትህ ለማቅረብ ማስረጃ አሰባሰብ ላይ መጎተት መኖሩ በስራቸው ላይ ችግር መፍጠሩን አንስተዋል።
በኢትዮ ቴሌኮም የፍቼ ቅርንጫፍ የመስመር ክፍል ሀላፊ አቶ ደግሰው ተስፋዬ በፍቼ ከተማ እና በአካባቢዋ በተደጋጋሚ በሚፈፀም ስርቆት የኢትዮ ቴሌኮም በሚሰጠው አገልግሎት ላይ ችግር መፍጠሩ ገልጸዋል፡፡በተለይም የኢትዮ ቴሌኮም የመስመር ሽቦ በህገወጥ መንገድ የኤሌክትሪክ መብራት አገልግሎት የሚያውሉ ግለሰቦች መበራከታቸው ለስርቆቱ አስተዋፆ እንዳደረገ እና ችግሩን ለመቅረፍ ከፌቼ ከተማ ፖሊስ ጋራ በጋራ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡
የፊቼ ከተማ መብራት ሀይል ዲስትሪክት ሀላፊ አቶ አዲሱ ደሰታ በበኩላቸው በህገ ወጥ መንገድ በየሰፈሩ እየተዘረጉ ያሉ መብራት ዝርጋታቸው ላይ ከመስሪያ ቤታቸው እውቅና ውጪ በመሆኑ እርምጃ ለመውሰድ ግብር ሀይል መቋቋሙን ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል፡፡
በሳምራዊት ስዩም