በሶማሊያ የሚገኘው የአፍሪካ ህብረት ሃይል በመጪው አመት መጨረሻ ሙሉ ለሙሉ ከሀገሪቱ ለመዉጣት የያዘዉን እቅድ ተከትሎ ቀስ በቀስ መዉጣት የጀመረ ሲሆን ሶስት ወታደራዊ ካምፖችን ለሶማሊያ ጦር አስረክቧል፡፡በሰኔ ወር መጨረሻ ወደ 2,000 የሚጠጉ ወታደሮችን ከሶማሊያ ለማስወጣት በአፍሪካ ህብረት ጦር እቅድ ተይዟል፡፡
ርክክብ የተካሄደው በመካከለኛው ሸበሌ ክልል ውስጥ በአዳሌ፣ ሚርታክዋ እና ሃጂ አሊ በሚባሉ የጦር ሰፈሮች ሲሆን በአፍሪካ ህብረት የተሰማራዉ የቡሩንዲ ጦር በስፍራዉ ነበረ፡፡በያዝነው አመት የአፍሪካ ህብረት ጦር ስድስት ወታደራዊ ካምፖችን ለሶማሊያ ጦር ያስረከበ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ አምስቱ በመካከለኛው ሸበል ግዛት ዉስጥ ይገኛሉ።
በዋና ከተማዋ ሞቃዲሾ በሄሊዋ ወረዳ የሚገኘው የመጀመሪያው የጦር ሰፈር በጥር ወር የሶማሊያ ጦር የተረከበ ሲሆን በብሩንዲ ሃይሎችም ይመራ ነበር።ምን ያህሉ የአፍሪካ ህብረት ወታደሮች ግን ከሶማሊያ እንደወጡ ህብረቱ ግልፅ አላደረገመ፡፡ሶማሊያ በአሁኑ ወቅት 19,000 የአፍሪካ ህብረት ወታደሮችን ለመተካት በኡጋንዳ፣ ኢትዮጵያ እና ኤርትራ አዳዲስ ወታደሮችን በማሰልጠን ላይ ትገኛለች፡፡
ይህ የሚያሳየዉ የሶማሊያ መንግስት በአልሸባብ ላይ ከፍተኛ ወታደራዊ ጥቃት ለመፈጸም በሁለተኛ ምዕራፍ ዝግጅት ላይ መሆኑን ነዉ፡፡ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት ያለው ታጣቂ ቡድኑ አልሻባብ በመቶዎች የሚቆጠሩ አዳዲስ ተዋጊዎቹን ሲመረቅ የሚያሳይ አዲስ ቪዲዮ ለቋል።
በስምኦን ደረጄ