
በቻይና ላይ የሚገኙ የበይነ መረብ ጠላፊዎች የአሜሪካ መንግስት ኤጀንሲዎች ጨምሮ ወደ 25 የሚጠጉ ድርጅቶችን የኢሜል አድራሻ ማግኘት ችለዋል ሲል ማይክሮሶፍት አስታዉቋል፡፡ግዙፉ የሶፍትዌሩ ድርጅት ማይክሮሶፍት በቻይና የበይነ መረብ ጠላፊዎች ኢሜይሎቻቸዉን የተወሰዱባቸዉን ኤጀንሲዎች ዝርዝር መረጃ ግን አላቀረበም።
ሆኖም የአሜሪካ የንግድ ሚኒስቴር ማይክሮሶፍት ስለ ጥቃቱ ማሳወቁን አረጋግጧል።የንግድ ዋና ፀሐፊ የሆኑት ጂና ሬይሞንዶ የበይነ መረብ ጠላፊዎች ጥቃት ከደረሰባቸው ግለሰቦች መካከል እንደሚገኙበት ዘገባዎች ጠቁመዋል።የዩናይትድ ስቴትስ የንግድ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እንደተናገሩት “ማንኛውም ተጨማሪ እንቅስቃሴ ከተገኘ አፋጣኝ ምላሽ እንሰጣለን” ሲሉም አክለዋል።
የዩናይትድ ስቴትስ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱም በመረጃ ጠላፊዎቹ ኢላማ ተደርጎ ነበር።በለንደን የሚገኘው የቻይና ኤምባሲ ለሮይተርስ የዜና ወኪል እንደገለፀው ክሱ የተሳሳተ መረጃ ነው ሲል የአሜሪካ መንግስትን “የአለም ትልቁ የመረጃ ጠለፋ መገኛ እና የአለም አቀፍ የሳይበር ሌባ” በማለት በአጸፋዉ ከሷል፡፡
በስምኦን ደረጄ