በኦሮሚያ ክልል በተጠናቀቀው የ2015 በጀት ዓመት ባለፉት 11 ወራት ውስጥ 3 ሺ 631 የትራፊክ አደጋዎች መከሰታቸውን የክልሉ ትራፊክ ቁጥጥር እና ደህንነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር የሆኑት ኮማንደር በላቸው ትኪ በተለይ ለብስራት ሬዲዮና ቲቪ ተናግረዋል፡፡ በደረሰዉ አደጋ 1ሺ 492 ሰዎች ህይወታቸዉን ሲያጡ፣ 1 ሺ ሰዎች ላይ ከባድ እና 1ሺ 28 ሰዎች ላይ ደግሞ ቀላል የአካል ጉዳት መድረሱን ገልፀዋል።
በአደጋዉም በአማካይ በየቀኑ የአራት ሰዎች ህይወት ማለፉ ተነግሯል።በተከሰተው አደጋ ከባድ የአካል ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች የተለያዩ የሰውነት ክፍሎቻቸውን ያጡ ፣በዊልቸር የሚንቀሳቀሱ እና ከፊሎቹ ደግሞ በደረሰባቸው አደጋ በተለያዩ ሆስፒታሎች አሁኑም የህክምና እየተሰጣቸው ድጋፍ መሆኑን ኮማንደሩ ተናግረዋል፡፡
ከደረሰዉ አደጋ ከፍተኛ ቁጥር የተመዘገበው በምእራብ አርሲ፣ ምስራቅ ሀረርጌ ፣ ምስራቅ ወለጋ ፣ምዕራብ ሸዋ ፣ጅማ፣ ሰሜን ሽዋ ዞኖች እንዲሁም ሱሉልታ፣ገላን፣ለገጣፎ ፣አዳማ ፣ቡራዩ እና ሰበታ ከተሞችና ክፍለ ከተሞች ላይ ናቸው።በአለም አቀፍ ደረጃ በየቀኑ በአማካይ 3 ሺ 7 መቶ ሰዎች በትራፊክ አደጋ ህይወታቸውን ያጡ ሲሆን ይህም በአመት ውስጥ በአጠቃላይ 1.3 ሚሊዮን ሰዎች ህይወታቸዉን እንደሚያጡ ጥናቶች ያመላክታሉ::
በተጨማሪም በአማካኝ 71 በመቶ የሚሆነው አደጋ የሚደርሰው በወንድ አሽከርካሪዎች ነው።
በተመሳሳይ በኦሮሚያ ክልል 95 በመቶ የተከሰተው አደጋ የደረሰው በወንድ አሽከርካሪዎች መሆኑ ተገልፆል፡፡
እንዲሁም 90 በመቶ የሚሆነው አደጋ በቀኑ ክፍለ ጊዜ የደረሰ ሲሆን 10 በመቶ የሚሆነው ደግሞ በሌሊቱ ያጋጠሙ መሆናቸው ተገልፆል።ከፍጥነት ወሰነ በላይ ማሽከርከር እና የአሸከርካሪዎች ጥንቃቄ ጉድለት፣ ያለ እረፍት ማሸከርከር ፣ለእግረኛ ቅድሚያ አለመስጠር ፣የቴክኒክ ችግር፣ አቅጣጫን መልቅቀ የአደጋዎቹ መንስኤዎች መሆናቸውን ኮማንደር በላቸው ትኪ ጨምረው ለብስራት ሬዲዮና ቲቪ ተናግረዋል፡፡
የደረሰው አደጋ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር በ233 አደጋዎች መቀነሱ ተገልፆል፡፡
በሳምራዊት ስዩም