
???? ልጁን ለማየት በርካታ ሰዎች ወደወረዳው እየተጓዙ ነው
በስልጤ ዞን ሁልባራግ ወረዳ ቢለዋንጃ ቀበሌ ከወትሮው በተለየ መልኩ ከአራት አመት በፊት ባቂ ሲከማ መሀመድ የተባለ ልጃቸው ህይወቱ እንዳለፈና ነሐሴ 28 ቀን 2015 ዓ.ም ከመንገድ ላይ ሰው አንስቶ እንዳመጣላቸው ቤተሰቦቹ መናገራቸውን የደቡብ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የሚዲያ ክፍል ኃላፊ ምክትል ኮማንደር ታጁ ነጋሽ ለብስራት ሬዲዮና ቴሌቪዥን ተናግረዋል።
በሌላ በኩል በሁሉም ነገሩ ተመሳሳይ የሆነ አብዲ ሄራቶ አቦዬ የሚባል ልጅ የጠፋባቸው ቤተሰቦች ከሁልባራግ ወረዳ ወራበት ሻማ አከባቢ ልጃችን ነው ሲሉ መምጣታቸዉ የገለፀዉ ፖሊስ ልጁ መስማትም ሆነ መናገር የማይችል በመሆኑ ነገሩን አስቸጋሪ አድርጎታል። ቢሆንም ሁለቱ ቤተሰቦች መተማመን የማይችሉ ከሆነ አስፈላጊዉ ምርመራና ማጣራት ይደረጋል ሲሉ ምክትል ኮማንደር ታጁ ጨምረው ለጣቢያችን ተናግረዋል።
ሁለቱ ቤተሰቦች መተማመን ስላልቻሉ ከአራት አመት በፊት ህይወቱ አልፎ ተቀብሯል የተባለዉ ታዳጊ መቃብር ተቆፍሮ የሟች አፅም መኖር አለመኖሩ ማረጋገጥና በህጋዊ መንገድ የዲኤንኤ ምርመራ እንደሚደረግ ፖሊስ አስታውቋል።
ያልተረጋገጠ መረጃ መሰራጨቱ ተከትሎ ልጁን ለማየት በርካታ ሰዎች በሞተር፣ በባለ ሶስት እግር ተሽከርካሪ በተለምዶ በባጃጅ ወደ ታዳጊዉ ቤተሰብ መንደር እየጎረፈ ይገኛል ተብሏል።
የወረዳ ፖሊስ ያልተጣራ መረጃ በማህበራዊ ሚዲያ የሚያሰራጩ ወገኖች ካልተገባ ድርጊታቸዉ እንዲቆጠቡ ሲል አሳስቧል።
በትግስት ላቀው