በትንሳኤ በዓል እለት የመጀመሪያው የሞት አደጋ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 ሀያት ጤና ጣቢያ አካባቢ በግንባታ ላይ ባለ ህንጻ ያጋጠመ ነው።እድሜው 35 የተገመተ አንድ የቀን ሰራተኛ በኤሌክትሪክ ተይዞ ህይወቱ ማለፉን የአዲስ አበባ እሳት እና አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት ቡድን መሪ አቶ ጉልላት ጌታነህ በተለይም ለብስራት ሬድዮ ተናግረዋል።አስከሬኑን ከሚገነባው ህንጻ ለማውረድ 40 ደቂቃ የጠየቀ ሲሆን የአደጋ ጊዜ ሰራተኞችን በብርቱ ፈትኗል።
ሁለተኛው የሞት አደጋ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 6 ቄራ በረት አካባቢ በትላንትናው እለት ከለሊቱ 9፡39 አጋጥሟል። እድሜው 55 ዓመት የሚገመት አንድ ጎልማሳ ወንዝ ውስጥ ገብቶ ህይወቱ አልፏል።
በሌላ በኩል በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ጨፌ ኮንዲሚኒየም አካባቢ ከምሽቱ 12 ሠዓት የጎርፍ አደጋ የደረሰ ሲሆን ጎርፍ ሰባት ቤቶች ላይ ጉዳት አደድርሷል።12 የአደጋ ጉፕዜ ሰራተኞች እና የአካባቢው ህብረተሰብ ባደረጉት ጥረት ቤቶቹ ላይ ጉዳት ሳይደርስ ማዳን መቻሉን አቶ ጉልላት ጨምረው ለብስራት ሬድዮ ተናግረዋል፡፡
በአዲስ አበባ ባለፉት ሶስት የበዓል ቀናት ምንም ዓይነት የእሳት አደጋ አላጋጠመም።
ትግስት ላቀው