
ከዝናባማዉ የሐምሌ ወር አንስቶ በሱዳን በጎርፍ መጥለቅለቅ አደጋ ከ80 በላይ ሰዎች መሞታቸውን የመንግስት ባለስልጣናት አስታዉቀዋል፡፡የሱዳን ብሔራዊ የሲቪል መከላከያ ምክር ቤት ቃል አቀባይ በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት እስካሁን 84 ሰዎች በጎርፍ አደጋዉ ህይወታቸዉን ሲያጡ 67 ሰዎች ደግሞ ክፉኛ ተጎድተዋል፡፡
ከሱዳን 18 አውራጃዎች መካከል ቢያንስ 14ቱ ላይ ጎርፉ ጉዳት ያደረሰ ሲሆን ከ30,000 በላይ ቤቶች ወድመዋል፡፡ሰብሎች እና የመሠረተ ልማት አዉታሮች ወድመዋል፡፡በመላ አገሪቱ በከባድ ዝናብ እና ጎርፍ የተነሳ ቢያንስ 102,000 ሰዎች ተጎድተዋል ሲል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባወጣዉ ሪፖርት አመላክቷል፡፡
ባለፈው 2020 ዓመት ጎርፍ በሱዳን ባስከተለዉ ዉድመት 100 ያህል ሰዎች ህይወታቸዉ ሲያልፍ እና ከ600,000 በላይ ሰዎች ተጎጂ አድርጓል፡፡ ከ100 ሺ በላይ ቤቶች መዉደማቸዉን ተከትሎ ለሶስት ወራት ብሔራዊ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁ ይታወሳል፡፡
በስምኦን ደረጄ