
በቤላሩስ ስደተኞች ለተፈጠረው ቀውስ ፕሬዝዳንት ፑቲን ተጠያቂ ናቸው ስትል ፖላንድ ተናገረች
የፖላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ፖላንድን ከቤላሩስ ጋር በሚያዋስነው ድንበር ላይ ለተፈጠረው የስደተኞች ቀውስ እጃቸው አለበት ሲሉ ከሰዋል።የቤላሩሱ አምባገነን መሪ የፑቲን የቅርብ አጋር ናቸው ቀውሱን ያቀነባበሩት እሳቸው ናቸው ሲሉ የፖላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ማቲውሽ ሞራዊኪ ተናግረዋል።
ቢያንስ 2000 ስደተኞች በቤላሩስ ፖላንድ ድንበር ላይ ይገኛሉ።የቤላሩሱ ፕሬዝዳንት አሌክሳንደር ሉካሼንኮ በአውሮጳ ህብረት የተጠለባቸውን ማዕቀብ ለመበቀል ሲሉ ስደተኞችን ሆን ብለው ወደ ፖላንድ ድንበር ልከዋል መባላቸውን ውሸት ነው በማለት ክሱን አጣጥለዋል።
አብዛኛዎቹ በድንበሩ ላይ የሚገኙት ስደተኞች ወንዶች ቢሆኑም ሴቶችና ህፃናትም አሉበት ተብሏል። ከመካከለኛው ምስራቅ እና ከእስያ ሀገራት የመጡ ስለመሆናቸውም ተነግሯል። በድንበሩ አካባቢ ያለው የሙቀት መጠን ከዜሮ በታች በመውረዱ በርካቶች ህይወታቸውን ማጣታቸው ሪፖርት ተደርጓል።
በድንበር ላይ 12ሺ ወታደሮችን በማሰማራት በቤላሩስ ያሉ ስደተኞች ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገቡ ፖላንድ ማድረጓን ተከትሎ ጠ/ሚ ሞራዊኪ ወታደሮቹን በትላንትናው እለት ጎብኝተዋል።ከጉብኝቱ በኃላ በፓርላማ በነበራቸው ስብሰባ ሩሲያና ቤላሩስ የአውሮጳ ህብረትን ለማተራመስ እየሞከሩ ነው ብለዋል።
በስምኦን ደረጄ