
ማላዊ የቀድሞ ቡጢኛ ማይክ ታይሰን የካናቢስ አምባሳደር እንዲሆንላት ጠየቀች❗️
ማላዊ የቦክስ ኮከብ ቡጢኛ ለነበረዉ ማይክ ታይሰን የሀገሪቱ የካናቢስ ሰብል ይፋዊ አምባሳደር እንዲሆን ጠይቃለች፡፡የማላዊ ግብርና ሚኒስትር ሎቢን ሎው ለታይሰን በጻፉት ደብዳቤ በማላዊ ካናቢስን ማምረት ህጋዊነት ሰዉነት በማግኘቱ አዲስ የስራ እድሎችን እንደሚፈጥር ተናግረዋል ።
የቀድሞ የአለም የከባድ ሚዛን ሻምፒዮን የነበረው ታይሰን ስራ ፈጣሪ ሲሆን በአሜሪካ በካናቢስ እርሻ ኢንቨስትመንት ላይ ተሰማርቷል፡፡ ነገር ግን በ1990 ዎቹ የቀድሞው ቦክሰኛ በጾታ ወንጀሎች ታስሮ ስለነበረ ይህ የአምባሳደር ጥያቄ ትችት ገጥሞታል፡፡
የካናቢስ ኢንቨስትመንት ዉስብስብ በመሆኑ ማላዊ ለብቻዋ የማይትወጣዉ መሆኑን የማላዊ የግብርና ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡የሀገሪቱ የግብርና ሚኒስቴር ገበሬዎች ካናቢስን ለመድኃኒትነት እንዲሁም ለኢንዱስትሪ አገልግሎት ብቻ እንዲያመርቱ ባለፈዉ ዓመት ፍቃድ መስጠቱ ይታወሳል፡፡
በስምኦን ደረጄ