የቅርስ ጥናት እና ጥበቃ ባለስልጣን አዋጅ ቅርስን ሆን ብሎ ያፈረሰ እና ያወደመ ለተለያየ አላማ ያዋለ እስከ 18 አመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ያስቀጣል በሚል ቢደነግግም የማስፈጸም ችግር መኖሩ በአዲስ አበባ የሚገኙ ቅርሶች እየወደሙ መሆኑን በባለስልጣኑ የቅርስ ጥገና እና እንክብካቤ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሮ ሰላማዊት ጌታቸው በተለይ ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል።
ከእውቅና ውጪ ፣በማታ እንዲሁም ከስራ ሰአት ውጪ ጉዳት እየደረሰበት በመሆኑ ከተማዋን ወደ ቅርስ አልባነት እየወሰዳት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ አሁን ላይ አንዳንድ አካላት ቅርስን ሆን ብሎ በተደጋጋሚ እሴት አልባ ለማድረግ አስበው ድርጊቱን እንደሚፈጽሙ ዳይሬክተሯ አንስተዋል፡፡ አዲስ አበባ ከ100 ዓመታት በላይ እድሜ አስቆጥራለች ካልን ማረጋገጫ ያሻል ማረጋገጫዎቿ ደግሞ ቅርሶቿ ናቸው እነሱን ካጣን ከተማዋ ስላስቆጠረችው እድሜ መናገር አመኔታ ያሳጣል ብለዋል፡፡
አሁን ላይ በአዲስ አበባ ቱሪዝም ቢሮ በኩል እንቅስቃሴዎች ያሉ ሲሆን ያፈረሰን አካል ህግ ፊት በማቅረብ የመሞገት ስራዎችን መጀመራቸውም አንስተዋል፡፡ ከወራት ወዲህ ነገሮቹ እየተረጋጉ ቢሆንም ቅርስ አውዳሚ ትውልድ መሆን የሚያሳፍር እንደመሆኑ ዘላቂ መፍትሄ በመንግስት በኩል ያሻል ሲሉ ወ/ሮ ሰላማዊት ጌታቸው ጨምረዉ ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል፡፡
ቤተልሄም እሸቱ