በደብረ ብርሃን ከተማ የሚገኙ ከሰሜን ሸዋ የተፈናቀሉ ተፈናቃዮች ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ወደ ቀያቸው እየተመለሱ መሆኑን ተገልጿል።
በተጨማሪም ከደቡብ ወሎ ጋር ተይይዞ የደሴ እና የኮምቦልቻ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው ለመመለስ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን የደብረ ብርሃን ከተማ ሰላም እና ደህንነት ፅ/ቤት ሀላፊ አቶ ዳንኤል እሸቴ በተለይ ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል፡
ተፈናቃዮቹ ከተገኘው ድል ጋር ተያይዞ ወደ ቀያቸው የመመለስ ሂደት ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ በመምጣቱ በደብረ ብርሃን ከተማ የተፈናቃዮቹ ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየቀነሰ መምጣቱን ነው ሀላፊው ለጣቢያችን የገለጹት፡
እንዲሁም በከተማው 65 ወንድ እና 38 ሴቶች በአጠቃላይ 103 ጸጉረ ልውጦች ተለይተው የምርመራ መዝገባቸው እየተጣራ ይገኛል።
ከተያዙት ጸጉረ ልውጦች ውስጥ 23ቱ ላይ በተለየ መንገድ ምርመራ እየተደረገባቸው እንዳለ እና በቅርቡም የክስ መዝገባቸው ወደ መደበኛ ፍርድ ቤት ሄዶ ውሳኔ እንደሚያገኝ ተገልጿል፡፡
ሳምራዊት ስዩም