
በደቡባዊ ሜክሲኮ በከባድ ተሽከርካሪ መገልበጥ ቢያንስ 53 ሰዎች ሲሞቱ በርካቶች ክፉኛ መቁሰላቸውን የመንግስት ባለስልጣናት አስታውቀዋል።ከመካከለኛው አሜሪካ የመጡ ከ100 በላይ ስደተኞችን ያሳፈረው ተሽከርካሪ በቺያፓስ ግዛት ውስጥ ሲገለበጥ ተስተውሏል።
ከአደጋው ስፍራ የወጡ ምስሎች ከተገለበጠው የጭነት ተሽከርካሪ አጠገብ በመንገድ ላይ በነጭ አንሶላ የተሸፈነ የሟቾች አስክሬን አመላክተዋል። የቺያፓስ ሲቪል ጥበቃ ኤጀንሲ ኃላፊ የሆኑት ሉዊስ ማኑዌል ጋርሺያ እንደተናገሩት በሜክሲኮ አስከፊ ከሆኑ የተሽከርካሪ አደጋዎች አንዱ በማለት፣ ቢያንስ 58 ሰዎች መቁሰላቸውን ገልፀዋል።
ከተጎጂዎች መካከል ሴቶች እና ህጻናት እንደሚገኙበት ተነግሯራ። ዜግነታቸው በይፋ ባይረጋገጥም የአካባቢው ባለስልጣናት በተሽከርካሪው ውስጥ ከነበሩት አብዛኛዎቹ ከሆንዱራስ እና ከጓቲማላ የመጡ ናቸው ብለዋል። መኪናው ወደ ቺያፓስ ግዛት ዋና ከተማ ቱክስትላ ጉቲዬሬዝ በሚወስደው ዋና መንገድ መታጠፊያ ላይ በፍጥነት እየተጓዘ ተገልብጧል።
የቺያፓስ ግዛት ከጎረቤት ሀገር ጓቲማላ ጋር የሚዋሰን ሲሆን ለሰነድ አልባ ስደተኞች ዋንኛ መሸጋገሪያ ነው።
በሚኪያስ ፀጋዬ