ዓመታዊ የቅዱስ ገብርኤልን በዓልን ጨምሮ የገና እና የጥምቀት በዓል ለማክበር ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡትን አንድ ሚሊየን ኢትዮጲያዉያን እና ትውልደ ኢትዮጵያን ወደ ሀዋሳ ከተማ ሲገቡ ያለ አንዳች የጸጥታ ችግር እንዲያሳልፉ ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን የሀዋሳ ከተማ ጸጥታ ቢሮ አሰታወቀ፡፡
በሀዋሳ ከተማ ያለው የጸጥታ ሁኔታ አስተማማኝ በመሆኑ የጠቅላይ ሚኒስትት አብይ አህመድ ጥሪ ተከትለው ወደሀገር ውስጥ ከሚገቡ እንግዶች ሰማንያ በመቶ የሚሆኑት ወደ ሀዋሳ ሀዋሳ ከተማ ይመጣሉ ተብሎ እንደሚገመት የሀዋሳ ከተማ ጸጥታ መምሪያ ኃላፊ አቶ መኩሪያ መኒሳ ለብስራት ሬድዮ ተናረዋል፡፡
የጸጥታ መዋቅሩ ከመከላከያ ሰራዊት ፣ከፌደራል ፖሊስ፣ ከክልሉ ልዩ ሀይል እና ከከተማ ፖሊስ የተውጣጣ መሆኑ ተገልጿል፡፡የሀዋሳ ከተማ ነዋሪዎች በሲዳማ በዓል መሰረት እንግዶችን ዳኦቡሹ ብሎ እንዲቀበል ጥሪ የቀረበ ሲሆን በከተማዋ የሚገኙ የንግዱ ማህበረሰብ ቢሆን በእንግዶች ላይ የዋጋ ጭማሪ እንዳያደርግ እየተሰራ ይገኛል፡፡
የቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ በዓል የፊታችን ማክሰኞ የሚከበር ሲሆን በድምቀት በሚከበርባቸው በሀዋሳ እና ቁልቢ በቂ ዝግጅት መደረጉ ተገልጿል፡፡
በትግስት ላቀዉ