
የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሀምዶክ ሀገሪቱ ወደ ዲሞክራሲ የምታደርገውን ደካማ ሽግግር ያደናቀፈውን ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ተከትሎ በፖለቲካዊ አለመግባባት የተነሳ ስልጣናቸውን ለቀዋል።በህዳር ወር ከጦር ኃይሎች ጋር የፖለቲካ ስምምነት የተፈራረሙት ሀምዶክ በትላንትናዉ እለት ምሽት በሱዳን ብሄራዊ ቴሌቭዥን በተላለፈ ንግግር አዲስ ስምምነት ላይ ለመድረስ በጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
ሀምዶክ በመልዕክታቸዉ “ኃላፊነቴን ለመመለስ ወስኛለሁ እናም ከጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ መልቀቄን ለመግለፅ እፈልጋለሁ፤ለዚህች ክቡር ሀገር ለሌላ ሰዉ እድል ለመስጠት ሱዳንን ወደ ሲቪል ዲሞክራሲያዊ ሀገር ለማሻገር እንዲረዳ ይህንን ዉሳኔ ወስኛለሁ ’‘ ሲሉ በቴሌቭዥን በተላለፈ መልዕክታቸዉ ተናግረዋል።የሀምዶክ ከስልጣን መልቀቅ የሀገሪቱን ፖለቲካ እጣ ፈንታ ወደ ጥርጣሬ ውስጥ ከቷል፡፡
የቀድሞ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባለስልጣን ሀምዶክ ከወታደራዊ አስተዳደር ነፃ የካቢኔ መንግስት እንዲቋቋም ባደረጉት ስምምነት በህዳር ወር ላይ ወደ ስልጣን መመለሳቸዉ ይታወሳል፡፡ይህዉ ድርድር ግን የዲሞክራሲ ንቅናቄ በሚያደርጉ አካላት ውድቅ መደረጉ ይታወሳል፡፡
በትላንትናዉ እለት በኦክቶበር 25 የተካሄደውን ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት በመቃወም የዲሞክራሲ ደጋፊ ሀይሎች የሚያደርጉትን ተቃዉሞ ለማብረድ በጸጥታ ሀይሎች በተወሰደ እርምጃ ቢያንስ ሁለት ሰዎችን መግደላቸውን የህክምና ቡድን አስታዉቋል።የዲሞክራሲ ንቅናቄ አካል የሆነው የሱዳን ዶክተሮች ማዕከላዊ ኮሚቴ በትላንትናዉ እለት በካርቱም በተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ከሟቾቹ መካከል አንዱ በጭንቅላቱ ላይ ተመቶ ህይወቱ ማለፉን ባወጣዉ መግለጫ አስታዉቋል፡፡
ሁለተኛው ሟች በካርቱም መንትያ ከተማ ኦምዱርማን ደረቱ ላይ በጥይት ተመቶ መገደሉ ሪፖርት ተደርጓል።የሱዳን የማህበራዊ ሚዲያ አንቂዎች 2022 ዓመት “የተቃውሞው ቀጣይነት ያለው ዓመት” ይሆናል ብለዋል ።ከጥቅምት አጋማሽ መፈንቅለ መንግስቱ በኋላ በተደረጉ ህዝባዊ ተቃውሞዎች ከ50 በላይ ሰዎች ተገድለዋል፡፡
በስምኦን ደረጄ