
የጌዴኦ ዞን በቦረና በተከሰተው ድርቅ የተጎዱ ከ10ሺህ በላይ ከብቶችን መረከቡን እና ባለዉ የግጦሽ መሬት ላይ ማሰማራቱን የዞኑ መንግስት ኮሚኒኬሽን ሀላፊ አቶ አብርሃም መኩሪያ በተለይ ለብስራት ራዲዮ ተናግረዋል።
የጌዴኦ ዞን ከብቶችን ለመታደግ በሚደረገው ጥረት በቦረና በተከሰተዉ ድርቅ 280 አባወራዎችን እና ከ10 ሺህ በላይ ከብቶችን ተቀብሎ በማስተናገድ ላይ ይገኛል።በተጨማሪም በድርቁ በከፍተኛ ደረጃ ለተጎዱ 3ሺህ ከብቶች የተለየ የህክምና ክትትል እየተደረገላቸው ይገኛል፡፡
የጌዴኦ ዞን ከ 6.2 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ የቁሳቁስ ድጋፍ አድርጓል። ዞኑ የከብት መኖ ፣ የህክምና እና የግብአት አቅርቦት ቡድን በማዋቀር ለተረከባቸዉ ከብቶች እንክብካቤም እያደረገ እንደሚገኝ የኮሚኒኬሽን ሀላፊው አቶ አብርሃም መኩሪያ ጨምረዉ ለብስራት ሬድዮ ተናግረዋል ።
ብስራት ራዲዮ ከዚህ ቀደም በሰራዉ ዘገባ በቦረና ከ180ሺህ በላይ ከብቶች በተከሰተዉ ድርቅ መሞታቸዉን መዘገቡ ይታወሳል።
በበረከት ሞገስ