ትናንት ጥር 15 ቀን 2014 ከሰዓት ወደ ሰቆጣ በጉዞ ላይ የነበረ የህዝብ ማመላለሻ መኪና ተገልብጦ የብዙ ሰዎች ህይወት ለህልፈት መዳረጉን የዋግ ኽምራ ዞን አስተዳደር አስታወቀ፡፡
የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪው መነሻውን ከእብናት/ባህር-ዳር አድርጎ ወደ ሰቆጣ በጉዞ ላይ እያለ በዓምደወርቅ ከተማ አስተዳደር አቅራቢያ ወደ ሰቆጣ አቅጣጫ “ፈጠቀው” ከሚባለው ቦታ ከመድረሱ በፊት ወደቀኝ አቦ ቤተ ክርስትያን ወይም በጉንዳይት በኩል በግምት ከ150 ሜትር በላይ ርቀት ላይ ገደል በመግባቱ ለጊዜው ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ የብዙ ሰዎችን ህይወት የነጠቀ አደጋ መከሰቱን አስተዳደሩ አስታውቋል።
እስከ አሁን ድረስም አስከሬን የማውጣት ሂደቱ ባለመጠናቀቁ በህዝብ ማመላለሻ አውቶብሱ ተሳፍረው የነበሩት እና በአደጋው የተጎዱ ተሳፋዎችን ቁጥር በውል ለማወቅ አለመቻሉም ተገልጿል፡፡
በአካባቢው በነበሩ ሰዎች በተገኘው መረጃ መሰረት ከገደሉ ርቀት እና ጥልቀት አኳያ በህይወት የሚተርፉ ሰዎች ይኖራሉ ብሎ ለማሰብ እንደሚከብድ የተገለፀ ሲሆን፣ የአደጋው መንስኤ ምንድን ነው የሚለውንም በትራፊክ ባለሞያች ከተጣራ በኋላ የሚገለፅ መሆኑም ተመላክቷል።