
በኢትዮጵያ የኩላሊት ህሙማን ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ የኩላሊት ህመምተኞች እጥበት በጎ አድራጎት ድርጅት አስታውቋል ።የበጎ አድራጎት ድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ሰለሞን አሰፋ ለብስራት ሬድዮ እንደተናገሩት ከሆነ ጥቂት የማይባሉ በጎ ፍቃደኛ ግለሰቦች ከህልፈታቸው በኋላ ኩላሊታቸውን ለመስጠት ቃል ቢገቡም በኢትዮጵያ ያለው የህግ ማዕቀፍ ቃላቸውን ተፈፃሚ እንዳይሆን እክል ፈጥሯል ሲሉ ገልፀዋል።
ኩላሊትን ጨምሮ ልብ እና ሳንባ የመሳሰሉትን የሰው ልጅ የውስጥ አካላት ሰዎች ከህልፈታቸው በፊት ቃል ገብተው መስጠት እንዲችሉ የሚፈቅድ ህግ እንዲኖር ለማድረግ ረቂቁን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን ለሚኒስትሮች ምክር ቤት አስገብተን ውጤት እየተጠባበቅን እንገኛለን ብለዋል።
ከእዚህ ባለፈ ከሁለት ዓመት በፊት በኮሮና ተህዋስ ወረርሽኝ ሳቢያ ተቋርጦ የቆየሁ የኩላሊት ንቅለ ተከላ በመስከረም እና ጥቅምት ወር ይጀመራል ተብሎ ቃል የተገባ ቢሆንም ተግባራዊ ባለመደረጉ ህሙማኑ ለከፋ ስቃይ እየተዳረጉ እንደሚገኙ አቶ ሰለሞን ተናግረዋል ።።
በአሁን ሰዓት በከፋ ስቃይ ላይ ለሚገኙ የኩላሊት ህሙማንን የሚሆን የገንዘብ ማሰባሰብ መረሃ ግብር ጥር 26 ቀን 2014 ዓ.ም በግዮን ሆቴል እንደሚካሄድ ተገልጿል።
የገንዘብ ማሰባሰብ መረሃ ግብሩ ተማሪዎችን ያካተተ በመሆኑ በጎ ፍቃደኞች ከሁለት ብር አንስቶ ማንኛውንም የገንዘብ መጠን መለገስ እንደሚቻል አቶ ሰለሞን አሰፋ ጨምረው ለብስራት ሬድዮ ተናግረዋል።
በናትናኤል ሀብታሙ