ዛሬ ሀምሌ 6 ቀን 2015 ዓ.ም ማለዳ 1:38 ሰዓት ላይ በሸገር ከተማ ቡራዩ ክፍለ ከተማ ጸራ ጽዮን እየተባለ በሚጠራዉ አካባቢ በንግድ ሱቆች ላይ የእሳት አደጋ ማጋጠሙን የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታውቃል።
በእሳት አደጋዉ የተለያየ የንግድ ስራ የሚከናወንባቸዉ 13 አነስተኛ በተለምዶዉ አርከበ ሱቆች በመባል የሚጠሩት መደብሮች መዉደማቸዉን የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ ለብስራት ሬድዮ ተናግረዋል።
የእሳት አደጋዉን ለመቆጣጠር አራት የአደጋ መቆጣጠር ተሽከርካሪ 30 የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች የተሰማሩ ሲሆን የእሳት አደጋዉ ተዛምቶ ተጨማሪ ጉዳት ሳያደርስ በቁጥጥር ስር ዉሏል። እንዱሁም አደጋዉን ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር 1 ሰዓት 24 ደቂቃ ፈጅቷል።
በሌላ በኩል ምሽት 5:24 ሰዓት በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 5 አየር ጤና አካባቢ በአንድ ግሮሰሪ ላይ በተነሳ የእሳት አደጋ መጠነኛ ጉዳት ደርሷል። በሁለቱም የእሳት አደጋዎች በሰዉ ላይ የደረሰ ጉዳት የለም ሲሉ የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ ጨምረዉ ለብስራት ሬድዮ ተናግረዋል።
በትግስት ላቀዉ