በኢትዮጵያ ከ5 አመት በታች የሆኑ ህፃናት የሞት ምጣኔ እ.አ.አ በ2005 ዓ.ም ከ1,000 በህይወት ከሚወለዱ ሕፃናት 123 ይመዘገብ ከነበረበት፣ እ.አ.አ በ2019 ወደ 59 ዝቅ ማድረግ መቻሉን ጤና ሚኒስቴር አስታውቃል፡፡
በተመሣሣይ ጊዜ ከአንድ ዓመት በታች ያሉ የሕፃናት ሞት ከ1,000 በህይወት ከሚወለዱ ከ 77 ወደ 47 ዝቅ ብሏል።እንዲሁም የጨቅላ ሕፃናት ወይም ከ0 እስከ 28 ቀን ሞት ከ1,000 በሕይወት ከሚወለዱ ከ 39 ወደ 33 ዝቅ ማረግ መቻሉን የእናቶች፣ ህጻናት እና አፍላ ወጣቶች ጤና አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶክተር መሰረት ዘላለም ለብስራት ሬድዮ እና ቴሌቭዥን ተግረዋል፡፡
በኢትዮጵያ ከ5 አመት በታች የህፃናት የሞት ምጣኔ ከክልል ክልል የሚለያይ መሆኑን የነገሩን ዶክተር መሰረት ከ1000 በህይወት ከሚወለዱ ህጻናት ከፍተኛ የሞት መጠን ያስመዘገበ ሶማሊ ክልል ሲሆን ይህም ከ1000ሺ ህጻናት 101 ህይወታቸውን የሚያጡ ሲሆን ዝቅተኛው በአዲስ አበባ ከተማ የተመዘገበ ሲሆን ከ1000ሺ ህጻናት 26 ሞት ማስመዝገቡ ተነግሯል፡፡
ከ5 ዓመት በታች የህፃናት ሞት መጠን የቀነሰ ቢሆንም ከዘላቂ የልማት ግቦችን አላማ አንፃር ከ1,000 በሕይወት ከሚወለዱ ህይወታቸው የሚያለፈውን ከ25 በታች ለማድረስ የበለጠ መስራት እንዳለበት ተጠቁማል፡፡
በትግስት ላቀው